መነሻ / ልምድ እና ተሞክሮ / መንግሥቱ የቆዳ ውጤቶች

መንግሥቱ የቆዳ ውጤቶች

ድርጅቱ የተመሠረተው በአቶ መንግሥቱ ሺፈራው በ2008 ዓ.ም. ነው። አቶ መንግሥቱ በቆዳ ውጤቶች፣ በቀበቶ እና በተለያዩ የጫማ ሥራዎች ላይ የሰላሣ ዓመት የሥራ ልምድ አካብተዋል።

 ድርጅቱ የሚያመርታቸው ምርቶች

  • የወንድ እና የሴት ጫማዎች
  • የህጻናት ጫማዎች
  • የወንድ ሽፍን እና ክፍት ጫማዎች
  • ቀበቶዎች
  • የተለያዩ የቆዳ ጌጣጌጦች

ማስተዋወቅ እና ማስፋፋት

አቶ መንግሥቱ ይህን ድርጅት ከመመሥረታቸው በፊት ትምህርት ቤት እያሉ ግማሽ ቀን ትምህርት ቤት ግማሽ ቀን ደግሞ ከቤተሰባቸው ጋር በመሆን የቆዳ ሥራ ይሠሩ ነበር። በዚህም በቂ ልምድ ካካበቱ በኋላ ትምህርታቸውን እንደጨረሱ አንድ የልብስ ስፌት መኪና እና ውጋቸው አንድ ሺህ ብር የሚገመቱ እቃዎችን ከቤተሰባቸው በመበደር ቀጥታ ወደ ሥራ ገብተዋል። አሁን ድርጅቱ አጠቃላይ የካፒታል አቅሙን ወደ አምስት መቶ ሺህ ብር ማሳደግ ችሏል። ድርጅቱ የሚያመርታቸውን ጫማዎች ከሁለት መቶ ብር እስከ አምስት መቶ ብር ድረስ ለገበያ እያቀረበ ይገኛል።

የድርጅቱ የማምረት አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ አሁን ላይ በአምስት ቀናት ውስጥ አራት ደርዘን ጫማ በጥራት አጠናቆ የማስረከብ አቅም አለው። ለዚህም ደግሞ የሚያመርታቸው ምርቶች በጣም በጥራት ስለሚመረቱ ነው እንጂ ሌላ በሦስት ቀናትም ማጠናቀቅ ይችላል ካስፈለገ።

ድርጅቱ ሥራዎቹን የሚያስተዋውቀው የቴሌግራም ቻናል በመጠቀም፣ በባዛር እና ቢዝነስ ካርድ በመጠቀም ሲሆን ጠቀም ያለ ሥራ ደግሞ በባዛር በኩል እንደሚያገኝ የድርጅቱ መሥራች ገልጸዋል። አቶ መንግሥቱ በተጨማሪ ደግሞ በከፍታ ፓኬጅ የቀረበውን የ2merkato.com የጨረታ አገልግሎትን ይከታተላሉ። ነገር ግን በብዛት የሚወጡ ጨረታዎች የሽፍን ጫማ ስለሆኑ እና ብዛት ስላላቸው እስካሁን ድረስ ጨረታውን እያዩ እራሳቸውን በማዘጋጀት ላይ ይገኛሉ።

ድርጅቱ ከተመሠረተ ጀምሮ ከነበሩት ችግሮች የገበያ እጦት ዋናው ነበር። ይህንንም ከሥራው ቅድመ ክፍያ በመውሰድ እና ቀሪውን ወደ ፊት እንዲከፍሉ በማድረግ ከተጠቃሚዎች ጋር አምነት በመፍጠር ያለውን የገበያ ችግር ሊፈታ ችሏል። እንዲሁም ሌላው ችግር ደግሞ የሙያተኛ ማነስ ነው፤ ይህ ማለት ጎበዝ ሠራተኞች ትልልቅ ድርጅቶች ጋር ስለሆነ የሚሠሩት አጥረት አለ። ይህንንም ችግር ደግሞ ቀለል ቀለል ያሉ ሥራዎችን ለሠራተኞች በመስጠት እና ጥንቃቄ የሚፈልጉትን ሥራዎች አንድ የተሻለ ሰው በመምረጥ ብዙ ሰዓት በመሥራት ችግሩን ሊፈቱ ችለዋል። እነዚህን ችግሮች በማለፍ ነው አሁን ድርጅቱ ለደረሰበት ደረጃ ሊደርስ የቻለው። አሁን ላይ ድርጅቱ ያሉትን የማሽን ቁጥሮች አራት ያደረሰ ሲሆን ሌሎች ለሥራ የሚጠቅሙ እቃዎችን አሟልቷል። እንዲሁም የምርት ጥራት ጨምሯል፤ በተጨማሪ ደግሞ ለዐሥር ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር የቻለ ድርጅት ሆኗል።

የኮቪድ ተፅዕኖ

የኮሮና ቫይረስ የነበረው ተፅዕኖ በጣም ከባድ ነበር። የኮሮና ወረርሽኝ መጀመርያ በተከሰተበት ወቅት ሁለት ወር ድርጅቱ ሥራ አቁሞ ነበር። ከሁለት ወር በኋላ ገባ ወጣ እያሉ ሥራ ስላልነበር አዳዲስ የጫማ ዲዛይኖችን በመንደፍ አሳልፈዋል። ነገሮች ከኮሮና የመጀመርያ ጊዜ ወዲህ በጣም ተቀይረዋል። ጥሬ እቃ የለም፤  ክፍለ ሀገር መሄድም እቃ መላክ አልተቻለም። ዕቃ አቅራቢ ነጋዴ ጋር ያለው የዋጋ አለመረጋጋት በጣም አስቸጋሪ ነው። በተጨማሪም አሁን የሰዉ እቃ የመግዛት ፍላጎት እና አቅም በጣም ቀንሷል።

ምክር እና እቅድ

አቶ መንግሥቱ አንድ ቢዝነስ ያለው ሰው የሚከተሉትን ስነ-ምግባሮች እንደሚያስፈልጉት ጠቅሰዋል፦ ሥራውን በፍቅር ይሥራ፤ ለሥራው ተገዢ ይሁን፤ ደንበኞችን በተቻለ መጠን ማክበር፤  ሥራን ለነገ ሳይልይ ዛሬ አጠናቅቆ ማስረከብ አለበት።

እንደ እቅድ ወደ ፊት ድርጅቱ ሌሎች የጫማ አይነቶች ለመሥራት እና በደንብ ለማስፋት እቅድ አለው። ይህም እቅድ የታቀደው 2merkato.com ለጥቃቅንና አነስተኛ ድርጅቶች ያዘጋጀው የከፍታ አገልግሎት ላይ የሚወጡ ጨረታዎችን በመከታተል እንደሆነ እና ወደ ገበያው ለመግባት ዝግጅት እንዲያደርጉ እንደረዳቸው አቶ መንግሥቱ ጠቅሰዋል።አገልግሎቱ በጣም ጥሩ ነው የአቅም ጉዳይ ነው እንጂ በደንብ እንደሚጠቅማቸው ያውቃሉ ወደ ፊት በደንብ እንደሚጠቀሙበት ገልፀዋል።

የድርጅቱን አገልግሎት መጠቀም የሚፈልጉ የድርጅቱን ስልክ በዚህ ሊንክ በመግባት ዓይተው መደወል ይችላሉ

ይህንንም ይመልከቱ

ሀሌታው ሀ ኅትመት እና ማስታወቂያ

ድርጅት የተመሠረተው በአቶ ዮናታን ታደሰ እና ሦስት መሥራች አባላት በ2012 ዓ.ም. ነው። ድርጅቱ አጠቃላይ የኅትመት …